የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለክልል ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊዎችና ሠራተኞች የሕግ ማዕቀፍ ሥልጠና ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሕግ ማዕቀፍ ላይ በማተኮር ለቦርዱ የክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎችና ሠራተኞች ሥልጠና የሰጠው ነሐሴ 10 እና 11 ቀን 2014 ዓ.ም ነው።
ሥልጠናው በቦርዱ አመራር አባል የሆኑት ፍቅሬ ገ/ሕይወት ንግግር ተከፍቷል። አመራሩ በንግግራቸው የቦርዱ የክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎችና ሠራተኞች እንዲሁም የምርጫ አስፈጻሚዎች በ6ተኛው ሀገራዊ ምርጫ የነበራቸውን አስተዋፅዖ በማንሳት ምሥጋና አቅርበዋል።
አያይዘውም ቦርዱ እንደ አዲስ የተቋቋመ በመሆኑ በጊዜው በርካታ እቅዶች ቢኖሩም ከጊዜና ከሁኔታዎች አንጻር የታቀደውን ሁሉ በሚፈለገው መጠን መፈፀም እንዳልተቻለ የጠቆሙ ሲሆን፣ አሁን ግን እነዚህን ጉዳዮች ለመተግበር አመቺ ሁኔታ ስለተፈጠረ በተለይ በቀጣይ ለሚደረገው ትልቅ ዐቅም ለሚጠይቀው የአካባቢ ምርጫ ይህ ሥልጠና የሚኖረውን አስተዋፅዖ አብራርተዋል።