የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሥነ ዜጋ ትምህርት ቀጣይነት ዙሪያ ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች እና ከባለድርሻ አካላት ጋር ምክክር አካሔደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሥነ ዜጋ ትምህርት ቀጣይነት ዙሪያ ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች እና ባለድርሻ አካላት ጋር ግንቦት 25 ቀን 2014 ዓ.ም. ምክክር አካሄደ፡፡ በቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ውብሸት አየለ ንግግር የተከፈተው የምክክር መድረኩ፤ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችና ተቋማት የሥነ ዜጋና የመራጮች ትምህርት ተሣትፎ ምርጫ በሚደረግባቸው ዓመታት ላይ ብቻ ተወሥኖ እንዳይቀር ግንዛቤ እንዲወሰዱ ለማድረግና በሥነ ዜጋ ትምህርት ቀጣይነት ላይ የቦርዱ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ሚና ላይ ግንዛቤ መፍጠር ዐላማው ያደረገ ሲሆን፤ መድረኩ ላይ ከቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ በተጨማሪ የቦርድ አመራር አባል የሆኑት አበራ ደገፋን (ዶ/ር) ጨምሮ የቦርዱ የጽ/ቤት ኃላፊዋ ሜላትወርቅ ኃይሉ ተገኝተውበታል። ከባለድርሻ አካላትም ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች በተጨማሪ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተወካዮችና የዘርፉ ባለሞያዎች፤ እንዲሁም የብዙኃን መገናኛ አካላት በተገኙበት ተካሂዷል።