የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፖለቲካ ፓርቲዎች የክርክር የተግባር ልምምድ የሚያደርጉበትን መድረክ ማካሄድ ጀመረ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ጊዜ ክርክር የተግባር ልምምድ የሚያደርጉበትን መድረክ ጥቅምት 11 ቀን 2018 ዓ.ም ማካሄድ ጀመረ። ቦርዱ በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ረቂቅ የጊዜ ሠሌዳውን አስመልክቶ፤ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በተወያየ ማግሥት የተጀመረውንና እስከ ጥቅምት 14 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን መድረክ በንግግር የከፈቱት የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ሲሆኑ፤ በንግግራቸውም የክርክር ልምምዱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ፖሊሲዎቻቸውንና ፕሮግራማቸውን ለሕዝብ የሚያቀርቡበትን ሥልት እንዲያዳብሩበት፤ ቦርዱ በቀጣይ በሚያወጣው ፕሮግራምም የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ያላቸውን ፕሮግራምና ፖሊሲ ለመራጩ ሕዝብ በመገናኛ ብዙኃን አማራጮች በይፋ ከማቅረባቸው በፊት ልምድ የሚያዳብሩበት ጠቃሚ መድረክ እንደሚሆን ያላቸውን ዕምነት ገልጸዋል።