የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለቀድሞ የቦርዱ ሥራ አመራሮች የምስጋና ሽኝት እንዲሁም ለአዲስ ተሿሚዎች የእንኳን ደኽና መጣችሁ መርኅ-ግብር አካሄደ።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ላለፉት ስድስት ዓመታት ያገለገሉት የቀድሞ የቦርድ ሥራ አመራር አባላት፤ ምክትል ሰብሳቢ ውብሸት አየለ፣ የቦርድ ሥራ አመራር አባላት ብዙወርቅ ከተተ እና ዶ/ር አበራ ደገፋ የምስጋና ሽኝት ሥነ-ሥርዓት፤ እንዲሁም የአዲስ ተሿሚ ሥራ አመራር አባላት፤ ምክትል ሰብሳቢ ተስፋዬ ነዋይ፣ የቦርድ ሥራ አመራር አባላት ተክሊት ይመስል እና ነሲም አሊን የአቀባበል ሥነ-ሥርዓት ተካሂዷል።
የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ እና የቦርድ ሥራ አመራር አባሉ ፍቅሬ ገ/ሕይወት፣ የቀድሞ የቦርድ ሥራ አመራር አባላት ቤተሰቦች፣ የቦርዱ የዋናውና የቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሠራተኞች እንዲሁም ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት የተካሄደው የምስጋና ሽኝት መድረክ ላይ በርካታ የቀድሞ ሥራ አመራሮችን ስኬት የሚያሳዩ አጫጭር ዶክመንተሪዎች የታዩ ሲሆን፤ በቦርዱና በሥራ ባልደረቦቻቸውም የአክብሮትና የምስጋና መግለጫ ሽልማቶች ለቀድሞ አመራሮችና ለቤተሰቦቻቸው ተበርክቷል።