የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እና የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች አጋርነት መድረክ አስፈላጊነት ላይ ውይይት ተካሄደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ግንቦት 5 ቀን 2017 ዓ.ም. ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች (ሲ.ማ.ድ) ጋር የሚኖር የአጋርነት መድረክ አስፈላጊነት ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሄደ። ውይይቱን በንግግር የከፈቱት የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ ሲሆኑ፤ በንግግራቸውም ምርጫ ቦርድ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምርጫን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ለሚኖራቸው ተሣትፎ ዕውቅና ከመስጠት አንሥቶ አብሮ እስከመሥራት የደረሰ ግንኙነት እንዳለው አስታውሰው፤ ይኽም ሲሆን ሚናን በመለየት ተባብሮ መሥራቱ የምርጫን ነፃና ገለልተኛ እንዲሁም ዲሞክራሲያዊነቱን በማረጋገጥ ረገድ ከፍ ያለ አስተዋፅዖ ያለው በመሆኑ እንደሆነ ተናግረዋል። በዚኽም መድረክ ላይ ማኅበራቱ በምርጫ ትምህርትም ላይ ባላቸውም ተሣትፎ ይሁን እንደታዛቢ በሚኖራቸው ኃላፊነት መሻሻል የሚገባቸውን እየለዩ መሄድና የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።