የ6ኛው ዙር ቀሪና ድጋሚ ምርጫ እንዲሳካ የማስተባባር እና የክትትል ሥራ ያከናወኑ የክትትል ቡድኖች የሥራ ሪፓርት ተገመገመ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰኔ13 ቀን 2013 ዓ.ም. እና መስከረም 20 ቀን 2014 ዓ.ም. 6ኛውን ሀገር አቀፍ ምርጫ ማካሄድ በማይቻልባቸው ምክንያቶች ምርጫ ሳያካሂዱ በቀሩት በቤንሻንጉል-ጉሙዝ፣ አፋር፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ እና ሶማሌ ክልሎች የተካሄዱ የቀሪና ድጋሚ ምርጫዎች እንዳይስተጓጓሉ ድጋፍና ክትትል እንዲያደርጉ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተዋቅረው፤ ስምሪት ተሰጥቷቸው የነበሩ 27 የክትትል ቡድኖችን የሥራ አፈፃፀም ሪፓርት የተገመገመበት መድረክ አካሄደ።
በመርሃ ግብሩ የማጠቃለያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ የክትትል (Monitoring) ቡድን አደራጅተን ማሰማራት ከጀመርን ጊዜ አንስቶ የቦርዱ ምርጫ የማስፈፀም ዋነኛ ተልዕኳችን አይነተኛ መሻሻል አምጥቷል፤ በሂደቱም አሠራሮቻችንን ዳግም ለመፈተሽ በርካታ ትምህርቶችን መቅሰም ችለናል ብለዋል።