የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች በምርጫ ሂደት ትርጉም ባለው አግባብ እንዲሳተፉ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የድርሻቸውን እንዲወጡ ተጠየቀ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአካታችነት ማዕቀፍ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች በ7ኛው ሀገር አቀፍ ጠቅላላ ምርጫ በመራጭነት እና በተመራጭነት የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እየሰራ ይገኛል።
ይህን ዕቅድ ዕውን ለማድረግ ቦርዱ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን የምርጫ ፍላጎት ለመለየት እና ተሳትፎ ለማሳደግ ኢስት አፍሪካ የተባለ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ቀጥሮ ሀገራዊ ጥናት በማስጠናት ላይ ይገኛል።
አጥኚ ድርጅቱ አጥንቶ ባቀረበው ረቂቅ የጥናቱ ግኝቶች ላይ ለመወያየት በተዘጋጀ የአንድ ቀን አውደ ጥናት ላይ መልዕክታቸውን ያስተላለፉት የቦርዱ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን በምርጫ ሂደት የማሳተፍ ትርጉም ያለው ስራ የቦርዱ ጏላፊነት ብቻ ሳይሆን፤ መንግስትን ጨምሮ የሁሉም ባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ አሠራር እና ትብብርን ይጠይቃል ብለዋል።