የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ከፌዴራልና ከክልል የመገናኛ ብዙኃን ለተውጣጡ ጋዜጠኞች ሥልጠና ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ከፌዴራልና ከክልል የመገናኛ ብዙኃን ለተውጣጡ የዜና ክፍል ኃላፊዎች፣ አርታኢያን እና ጋዜጠኞች በገለልተኛ እና ሚዛናዊ የሚዲያ ዘገባ እና ኃቅን (እውነታን) በማረጋገጥ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የአንድ ቀን የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ሰጠ።
በሥልጠናው የመክፈቻ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ ምርጫ ለሀገራችን ዲሞክራሲ ማበብ ዋና የማዕዘን ድንጋይ በመሆኑ የመገናኛ ብዙኃን የምርጫ ሂደት አዘጋገብ ከስሜት እና ከወገንተኝነት የፀዳ ሊሆን ይገባል ብለዋል።