የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሴት ፖለቲከኞች በ7 ኛው ሀገራዊ ምርጫ የሚኖራቸውን ተሣትፎ ለማሳደግ የሚያስችል የዐቅም ግንባታ ሥልጠና ሠጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተቋማዊ ኃላፊነቱን ሲወጣ ትኩረት ከሚሰጣቸው ተግባራት አንዱ የሥርዓተ-ፆታና ማኅበራዊ አካታችነት ተጠቃሽ ነው። ቦርዱ ሴት ፖለቲከኞች በ7 ኛው ሀገራዊ ምርጫ የሚኖራቸውን ተሣትፎ ለማሳደግ በማሰብ መስከረም 19-20 ቀን 2018 ዓ.ም. የዐቅም ግንባታ ሥልጠና ሠጠ፡፡ የመድረኩን መክፈቻ ንግግር የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ያደረጉ ሲሆን፤ በንግግራቸውም ቦርዱ ሴቶችና እና አካል ጉዳተኞች በምርጫ ላይ የነቃ ተሣትፎና የጎላ ድርሻ እንዲኖራቸው የሚያበረታቱ ድንጋጌዎች በሕግ-ማዕቀፎቹ እንዲካተቱ ከማድረግ ባሻገር፤ በርካታ የዐቅም ግንባታ ሥልጠናዎችንና ድጋፎችን እየሰጠ እንደሚገኝ አስታውሰው፤ ይህም ሥልጠና በ7 ኛው ሀገራዊ ምርጫ የነቃ ተሣትፎ እንዲኖራቸው እንደሚያስችል ያላቸውን ዕምንት ገልጸዋል።