የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በወላይታ ሶዶ እና አርባምንጭ ከተሞች የክርክር መድረክ አካሔደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እና የምርጫ ሂደቶች ዙሪያ ዜጎችን ለመድረስ ያስችለዉ ዘንድ የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን እየሠራ ይገኛል፡፡ በመሆኑም ቦርዱ ድሪም ፎር ዴቨሎፕመንት ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ከተባለ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅት ጋር በመተባበር በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፡ ወላይታ እና አርባ ምንጭ ከተሞች በተማሪዎች፣ አካል ጉዳተኞች እና ሴቶች መካከል ሶስት የክርክር መድረክ አካሂዷል፡፡ የክርክሩ ጭብጡም በሶስት ርዕሰ-ጉዳዮች ዙሪያ ላይ ያተኮረ ሲሆን እነርሱም፡ ለሀገር ህልዉና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ግዴታ ነዉ ወይስ አይደለም?፣ማህበረሰቡ ስለ አካል ጉዳተኞች ያለዉ የተዛባ አስተሳሰብ አካል ጉዳተኞች በምርጫ ዙሪያ እኩል ተሳትፎ እንዳይኖራቸዉ አድርጓል ወይስ አላደረገም?፣ ሴቶች በምርጫ ወቅት በመምረጥ ነው ወይስ በመመረጥ የተሻለ ተሳትፎ የሚኖራቸዉ? በሚሉ የመከራከሪያ ሀሳቦች ዙሪያ ነዉ፡፡