ቦርዱ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ ፖለቲካ ፓርቲዎችን የምርጫ መወዳደሪያ ምልክት ይፋ ባደረገበት መድረክ ላይ ፓርቲዎች የምርጫ ሥነ-ምግባር ደንብ ፈረሙ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባሳለፍነው ሣምንት መጠናቀቂያ ባዘጋጀው መድረክ ላይ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ ፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ሥነ-ምግባር ደንብ ፈረሙ። ፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት ተወካዮች እንዲሁም መገናኛ ብዙ`ኃን በተገኙበት፤ 48 ፖለቲካ ፓርቲዎች ለምርጫ የሚወዳደሩባቸውን ምልክቶች ይፋ ለማድረግ የተዘጋጀውን መድረክ በንግግር የከፈቱት የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ሲሆኑ፤ በንግግራቸውም ቦርዱ የፖለቲካ ፓርቲዎችን የምርጫ መወዳደሪያ ምልክት ይፋ እስከሚያደርግበት ጊዜ ድረስ በነበረው የቅድመ-ምርጫ ተግባራቱ ምን ሲያከናውን እንደነበር ማብራሪያ ሰጥተዋል። የሥነ-ምግባር ደንቡን አስፈላጊነት አስመልክቶ ባደረጉት ንግግርም ምርጫ ነፃ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ ሆኖ የሚከናወነው ሁሉም ፓርቲ ሕግን አክብሮ ኃላፊነቱን ሲወጣ እንደሆነ፤ የምርጫው ስኬትም የሚረጋገጠውም ቦርዱ ለብቻው በሚያደርገው ጥረት ሣይሆን ሁሉም ባለድርሻ አካላት ዕኩል ኃላፊነቱን መወጣት ሲችል እንደሆነ በአጽንዖት ተናግረዋል።