የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በበጎ ፈቃደኝነት ለሚሠማሩ ወጣቶች ሥልጠና ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የተለያዩ የቅድመ ምርጫ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ከነዚኽም ተግባራት አንዱ ዜጎች በዕውቀት ላይ የተመሠረት ምርጫን እንዲያደርጉ የሚያስችላቸውን የሥነ ዜጋ እና የመራጮች ትምህርት መስጠት በዋንኛነት ይጠቀሳል። በመሆኑም የቦርዱ የሥነ ዜጋ እና የመራጮች ትምህርት ሥራ ክፍል ከቦርዱ የክልል ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ጋር በመተባበር አዲስ አበባ እና በድሬደዋ ከተማ መስተዳደሮችን ጨምሮ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ በጋምቤላ፣ በሐረሪ፣ በአፋር፣ በሶማሊ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ፣ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ፣ እና በሲዳማ ክልሎች በመራጮች ትምህርት እና በመረጃ ሥርጭት ዘመቻ ሥራዎች ላይ ለሚሣተፉ 775 በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች የሁለት ቀናት ሥልጠና ሰጥቷል።