የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በቀጠናዊ የምርጫ ሥጋት አስተዳደር ልምድ ልውውጥ አውደ ጥናት ላይ ተሣተፈ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአዲስ አበባ በተካሄደው በቀጠናዊ የምርጫ ሥጋት አስተዳደር ልምድ ልውውጥ ላይ ተሣተፈ። ነሐሴ 20 እና 21 ቀን 2016 ዓ.ም. በተካሄደው ቀጠናዊ ልምድ ልውውጥ አውደ ጥናት ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአራት ሀገራት ማለትም ከኬንያ፣ ቦትስዋና፣ ማላዊና ሴራሊዮን የመጡ የምርጫ ቦርድ አመራሮችና ባለሞያዎች የተሣተፉ ሲሆን፤ የልምድ ልውውጥ መድረኩም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ተጀምሯል። ሰብሳቢዋ በመክፈቻ ንግግራቸው ይኽ ቀጠናዊ የሥጋት አስተዳደር የልምድ ልውውጥና ሥልጠና ሀገራቱ በምርጫ ጉዳይ ላይ ያላቸውን ዕውቀት፤ልምድ እንዲለዋወጡና አንዳቸው ከሌላቸው የተሻለ ተሞክሯቸውን እንዲወስዱ የሚያስችል መሆኑን፤ ይኽም እርስ በርስ በመደጋገፍ በጋራ ለማደግ እንደሚያስችል ገልጸዋል።