የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በወላይታ ዞን ለሚያካሄደው የድጋሚ ሕዝበ ውሣኔ የምርጫ አስፈጻሚዎች ሥልጠና ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 12 ቀን 2015 ዓ.ም በወላይታ ዞን የሚያካሄደው የድጋሚ ሕዝበ ውሣኔ ላይ ለሚሣተፉ በየደረጃው ለሚገኙ የምርጫ አስፈጻሚዎች ሥልጠና ሰጠ። ከግንቦት 16 ቀን እስከ ግንቦት 21 ቀን 2015 ዓ.ም በተሰጠው ሥልጠናም የሥራ ትውውቅ፣ የውጤት ማመሳከር፣ የማዳመርና የይፋ አደራረግ ላይ ያተኮረ ሥልጠና ለዞንና ለማዕከል አስተባባሪዎች የተሰጠ ሲሆን፤ ለመሥክ አሠልጣኞችም እንዲሁ የአሠልጣኞች ሥልጠና በሶዶ ከተማ ተሰጥቷል።
በተጨማሪም ቦርዱ በወላይታ ዞን ውስጥ በተቋቋሙ 12 ማስተባበሪያ ማዕከላት ላይ ለ3608 የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚዎች በሁለት ዙር ሥልጠና በመስጠት ላይ የሚገኝ ሲሆን፤ የመጀመሪያው ዙር ሥልጠና ከግንቦት 23 እስከ ግንቦት 25 ቀን 2015 ዓ.ም ሲሰጥ፤ የሁለተኛ ዙር ሥልጠናም እንዲሁ ከግንቦት 26 እስከ ግንቦት 28 ቀን 2015 ዓ.ም የሚሰጥ ይሆናል።