የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቦርድ አመራር አባላት ሰኔ 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ምርጫ በሚካሄድባቸው አካባቢዎች የምርጫ ሥራዎችን በተመለከተ የመስክ ምልከታና ከባለድርሻ አካላት ጋር ለሁለት ቀናት የቆየ ምክክር አካሄዱ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የ6ኛው ዙር የጠቅላላ እና የድጋሚ ምርጫ ባልተካሄደባቸው የቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ የአፋር፣ የሶማሌ እና የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ሰኔ 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ለሚያካሂደው ምርጫ የተለያዩ የቅድመ-ምርጫ ተግባራትን በማከናወን ላይ መሆኑ ይታወቃል። ይህንንም ተከትሎ የመራጮች ምዝገባ ከሚያዚያ 21 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ በመከናወን ላይ በሚገኝባቸው በቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ በአፋር እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች የቦርዱ የበላይ ኃላፊዎች የመሥክ ጉብኝት እና ውይይት ከግንቦት 7-8 ቀን 2016 ዓ.ም. አካሂደዋል፡፡
በመስክ ጉብኝቱ በምርጫ ክልሎቹ ላይ እየተከናወነ ያለውን የምርጫ ነክ ሥራዎች ምን እንደሚመስሉ ከመመልከታቸው በተጨማሪ፤ በምርጫ ጣቢያዎቹ በመከናወን ላይ ያለውን የመራጮች ምዝገባ አጠቃላይ ሁነትን የተመለከቱ ሲሆን በየምርጫ ጣቢያዎቹ በሥራ ላይ ከነበሩ ከመራጮች ምዝገባ አስፈጻሚዎች ጋር ውይይት ተደርጓል።