የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች አካታችነትን በተመለከተ ሥልጠና አካሄደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መስከረም 14 ቀን 2017 ዓ.ም. የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች አካታችነትን በተመለከተ ሥልጠና አካሄደ። ይኽን ሁሉም የቦርዱ ሥራ ክፍል ኃላፊዎችና ከፍተኛ ባለሞያዎች የተሣተፉበትን ሥልጠና በንግግር ያስጀመሩት የቦርድ አመራር አባሏ ብዙወርቅ ከተተ ሲሆኑ፤ በንግግራቸውም የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች አካታችነት ሲባል ተፈናቃዮቹ እንደ መራጭ ያላቸውን መብት በማረጋገጥ ሳንወሠን እነሱን ዕጩ ተመራጭ ሆነው ጭምር እንዲመጡ የሚያስችል ሥራ መሠራት ጭምር እንደሆነ ተናግረዋል። ይኽም ሲባል የተፈናቃዮቹን ተሣታፊነት ለማረጋገጥ በወጡ ድንጋጌዎች መሠረት መሥራት ብቻ ሣይሆን የተለያዩ መለኪያዎችን በማስቀመጥ የሕጎቹን ተፈጻሚነት ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል። አክለውም ቦርዱ በቅርቡ ባስተዋወቀው የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅዱ ላይ “ራዕይ” እና “ቁልፍ ዕሴቶች” ብሎ ከዘረዘራቸው ውስጥ አካታችነት አንዱ እንደሆነና ለቦርዱ አካታችነት ትልቁ ትኩረቱ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች ጋር የምስጋና እና የልምድ ልውውጥ አካሄደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች ጋር የምስጋና እና የልምድ ልውውጥ መድረክ አካሄደ። ቦርዱ በ6ኛው ሀገራዊ የቀሪና ድጋሚ ምርጫ በአፋር፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝ፣ በሶማሌ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ዜጎች ስለዴሞክራሲያዊ ምርጫ እና ሂደቶች ግንዛቤ እንዲጨብጡ የስነ ዜጋ እና መራጮች ትምህርት እንዲያገኙ ብሎም በተለያዩ የስነ ዜጋ ትምህርት እሳቤዋች ዙሪያ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር የክርክር መድረኮች በማዘጋጀት በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ሂደት የክርክር ባህል እንዲጎለብት የላቀ አስተዋፅኦ ላበረከቱ የሲቪል ማኅበራቱ የምስጋና እና የልምድ ልውውጥ አካሂዷል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የአካል ጉዳተኞች አካታችነት ላይ ሥልጠና አካሄደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቦርዱ ሥራ ክፍል ኃላፊዎችና ከፍተኛ ባለሞያዎች የተሣተፉበትን ሥልጠና መርኅ-ግብር መስከረም 8 እና መስከረም 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ለሁለት ቀናት የአካል ጉዳተኞች አካታችነት ላይ ሥልጠና አካሄደ። ስልጠናዉን በንግግር ያስጀመሩት የቦርድ አመራር አባል የሆኑት ፍቅሬ ገ/ሕይወት ሲሆኑ፤ በንግግራቸውም ቦርዱ በተለይም በምርጫ ወቅት ትኩረት ሠጥቶ ከሚሠራባቸው ጉዳዮች ውስጥ የአካል ጉዳተኞች አካታችነት ከዋነኞቹ እንደ አንዱ የሚጠቀስ መሆኑን፤ ይኽም ሥልጠና ቦርዱ ለጉዳዩ የሚሰጠው ትኩረት በምርጫ ወቅት ብቻ የተገደበ ላለመሆኑ ማሳያ ነው ሲሉ ተናግረዋል። አመራሩ፤ በተጨማሪም አካል ጉዳተኛ የማኅበረሰብ ክፍሎች በምርጫ ወቅት በበቂ ላለመሣተፋቸው ምን ዓይነት ተግዳሮቶች አሉባቸው የሚለውን በመለየት የመፍትሔውም አካል መሆን እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በብሬይል የተዘጋጁ የተለያዩ የኅትመት ውጤቶችን ለኢትዮጵያ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መጻሓፍት አገልግሎት አስረከበ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከምርጫ ጋር ተያያዥነት ባላቸው በአምስት የተለያዩ አርእስቶች የተከፋፈሉ የብሬይል ብሮሸሮችንና ዐዋጆችን ለኢትዮጵያ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መጻሕፍት አገልግሎት ነሐሴ 24 ቀን 2016 ዓ.ም. አስረከበ። በብሬይል ከተዘጋጁት ኅትመቶች ውስጥ ዴሞክራሲ እና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት፣ አካታች የሆነ የምርጫ ሂደት፣ ምርጫ በኢትዮጵያ፣ የኢትዮጵያ የምርጫ ሥርዓት እና ሰላማዊ ምርጫ በኢትዮጵያ የሚሉ አርእስቶች ይገኙበታል። ቦርዱ በተጨማሪም በብሬይል የተዘጋጀ ‘የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ-ምግባር ዐዋጅ 1162/2011’ን ለአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ አበርክቷል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በቀጠናዊ የምርጫ ሥጋት አስተዳደር ልምድ ልውውጥ አውደ ጥናት ላይ ተሣተፈ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአዲስ አበባ በተካሄደው በቀጠናዊ የምርጫ ሥጋት አስተዳደር ልምድ ልውውጥ ላይ ተሣተፈ። ነሐሴ 20 እና 21 ቀን 2016 ዓ.ም. በተካሄደው ቀጠናዊ ልምድ ልውውጥ አውደ ጥናት ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአራት ሀገራት ማለትም ከኬንያ፣ ቦትስዋና፣ ማላዊና ሴራሊዮን የመጡ የምርጫ ቦርድ አመራሮችና ባለሞያዎች የተሣተፉ ሲሆን፤ የልምድ ልውውጥ መድረኩም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ተጀምሯል። ሰብሳቢዋ በመክፈቻ ንግግራቸው ይኽ ቀጠናዊ የሥጋት አስተዳደር የልምድ ልውውጥና ሥልጠና ሀገራቱ በምርጫ ጉዳይ ላይ ያላቸውን ዕውቀት፤ልምድ እንዲለዋወጡና አንዳቸው ከሌላቸው የተሻለ ተሞክሯቸውን እንዲወስዱ የሚያስችል መሆኑን፤ ይኽም እርስ በርስ በመደጋገፍ በጋራ ለማደግ እንደሚያስችል ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ‘ለትንሳኤ ስርዓት ቓንጪ ሓቂ’ የክልላዊ ፖለቲካ ፓርቲ የምዝገባና የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ‘ለትንሳኤ ስርዓት ቓንጪ ሓቂ’ የክልላዊ ፖለቲካ ፓርቲ የምዝገባና የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ከሐምሌ 29 እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2016 ዓ.ም. በጋና አክራ በአፍሪካ ሴት የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢዎች መካከል በተካሄደው በስትራቴጂካዊ የልምድ ልውውጥ መድረክ ላይ ተሣተፉ
የመድረኩ ዐላማም በምርጫ አስተዳደር አመራርነት ባሉ ሴት የቦርድ ሰብሳቢዎች መካከል የአቻ ላቻ ትብብርና ትሥሥር መፍጠር፤ እንዲሁም በአፍሪካ ደረጃ የሚያጋጥሙ ውስብስብ የምርጫ ዐውዶችን መልስ በመስጠት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለማንበር አስቻይ ሁኔታዎችን እንዴት መፍጠር ይቻላል የሚሉት ይገኙበታል። በአፍርካ ደረጃ ዘጠኝ ሴት የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢዎች ሲኖሩ፤ ኢትዮጵያ ከነዚኽ ሀገራት ውስጥ ተጠቃሽ ናት።