የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የመራጮች ምዝገባ ሂደት አፈጻጸምና አጠቃላይ የኦፕሬሽን ሂደቶች እንዲሁም መጪ ሁነቶችን የተመለከተ ውይይት አካሄደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ግንቦት 7 ቀን 2013 ዓ.ም ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የመራጮች ምዝገባ ሂደት አፈጻጸምና አጠቃላይ የኦፕሬሽን ሂደቶችን እንዲሁም ቀጣይ የምርጫ ተግባራትን የተመለከተ ብዙኃን መገናኛ አካላት በተገኙበት ውይይት አካሂዷል። የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር የተከፈተው መድረክ የድምፅ መስጫ ወረቀት ኅትመት፣ የሎጀስቲክ ማጓጓዝ፣ የመራጮች ምዝገባ ሂደትና የተለያዩ ተግዳሮቶች ከነተሰጡባቸው መፍትሔዎች ጭምር ቀርበውበታል። በሎጀስቲክ ማጓጓዝ ወቅት የተፈጠሩ መስተጓጎሎች፣ በአንዳንድ አካባቢዎች የተስተዋሉ የምርጫ ጣቢያዎች በጊዜ አለመከፈትና የተከፈቱት ሲሞሉም በአፋጣኝ ንዑስ ጣቢያዎችን ለመክፈት ከክልልና ከከተማ መስተዳደሮች ጋር በመነጋገር መፍትሔ ለመስጠት እንደተሞከረ ሆኖም ግን በሚፈለገው ፍጥነት ቦታዎቹን ማግኘቱ ቀላል እንዳልነበረ ተገልጿል።