Skip to main content

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለሚያካሄደው ሕዝበ ውሳኔ የ541 ሚሊዮን ብር የበጀት ጥያቄ አቀረበ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደቡብ ብ/ብ/ሕ/ክልላዊ መንግሥት ውስጥ ለሚያካሂደው ሕዝበ ውሣኔ ማስፈጸሚያ የሚያስፈልገውን የአምስት መቶ አርባ አንድ ሚልዮን ሁለት መቶ ሰባ ሺህ አንድ መቶ አራት ብር ከሰማንያ ሁለት ሳንቲም (የ541,270,104.82) በጀት ያቀረበው ለኢፌዴሪ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ነው።

ቦርዱ በደቡብ ብ/ብ/ሕ/ክልላዊ መንግሥት ሥር የሚገኙ ስድስት ዞኖች ማለትም የጋሞ፣ ጎፋ፣ ወላይታ፣ ጌዲዮ፣ ኮንሶና፣ ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም አምስት ልዩ ወረዳዎችን እነዚሁም የቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ባስኬቶ፣ አሌ ልዩ ልዩ ወረዳዎች ላይ ሕዝበ ውሳኔ እንደሚያካሄድ ይታወቃል።

ቦርዱ በተጠቀሱት ዞኖችና ልዪ ወረዳዎች ላይ ሕዝበ ውሣኔ በማደራጀት ውጤቱን እንዲያሳወቅ በፌዴሬሽን ምክር ቤት የተጠየቀው ነሐሴ 12 ቀን 2014 ዓ.ም. በተጻፈ ደብዳቤ ሲሆን፤ በዚህም መሠረት ቦርዱ የሕዝብ ውሣኔውን ለማከናወን የሚያስፈልጉ ዝርዝር ተግባራትን በማካተት የድርጊት መርኅ ግብር አዘጋጅቶ አቅርቧል።

በሕዝበ ውሣኔው የድርጊት መርኅ ግብሩ ላይ የተጠቀሱትን አጠቃላይ ተግባራት ተፈጻሚ ለማድረግም የሚያስፈልገውን በጀት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርቧል።

Share this post