መግቢያ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከምርጫ ሂደት መካከል ዋና የሆነውን የመራጮች ምዝገባን እያከናወነ ይገኛል። በዚህም መሰረት እስካሁን የተመዘገቡ መራጮች ቁጥር ጊዜያዊ 31,724,947

• ወንድ 54%

• ሴት 46 %

የመራጮች ምዝገባ የሚደረግባቸው ጣቢያዎች ቁጥር 43,017

በመራጮች ምዝገባ ወቅት ያጋጠሙ ችግሮች

የመራጮች ምዝገባ በሚከናወንበት ወቅት ያጋጠሙ ዋና ዋና ችግሮች

- የመራጮች ምዝገባ ዘግይቶ መጀመር (በቁሳቁስ ስርጭት የተነሳ)

- የመራጮች ምዝገባ በመጀመሪያዎቹ ሳምንታት የተመዝጋቢዎች ቁጥር ዝቅተኛ መሆን

- የመራጮች ምዝገባ ከተጀመረ በኃላ የምርጫ ጣቢያዎች እና የተመዝጋቢዎች አለመመጣጠን በተለይ በአዲስ አበባ በጋራ መኖሪያ ቤቶች

- የአስፈጻሚዎች ክፍያ መዘግየት

- በተወሰኑ ቦታዎች ( በተለይ በአዲስ አበባ) የአስፈጻሚዎች ሃላፊነትን በአግባቡ አለመወጣት

- በጸጥታ ችግር የተነሳ የመራጮች ምዝገባ ማድረግ ባልተቻለባቸው ቦታዎች በልዩ ሁኔታ የሚደረግ መሆኑ

የመራጮች ምዝገባ ላይ ላጋጠሙ ችግሮች የተሰጡ መፍትሄዎች

- የመራጮች ምዝገባ ቀናትን ማራዘም

- የመራጮች ምዝገባ የቁሳቁስ ስርጭትን አስመልክቶ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር ትብብርን ለማጠናከር ሙከራ ማድረግ

- የመራጮ ምዝገባ መልእክቶችን እና መረጃዎችን ማሰራጨት ስራን መጨመር (አጭር የስልክ መልእክቶች፣ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ትብብር፣ የሲቪል ማህበራት ቅስቀሳ… ወዘተ)

- ከፓርቲዎች እና ከዜጎች (በ778 ነጻ የስልክ መስመር) የሚመጡ ጥቆማዎችን ከምርጫ ኦፕሬሽን ስራዎች ጋር በማቀናጀት መፍትሄ መስጠት

- የጸጥታ ችግር ባለባቸዉ ቦታዎች ልዩ እቅድ እና ዝግጅት በማድረግ ከየክልሎቹ የጸጥታ ተቋማት ጋር በመተባበር የአስፈጻሚዎች ስልጠና እና የቁሳቁስ ስርጭት የተከናወነ ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ የመራጮች ምዝገባ ከሚያዝያ 29 ጀምሮ እንዲከናውንባቸው ተወስኗል (4ቱ ወለጋ ዞኖች (24 ምርጫ ክልሎች)፣ ካማሽ (4 ምርጫ ክልሎች) እና አማራ ክልለ ኦሮሞ ብሔረሰብ ልዩ ዞን (3 ምርጫ ክልሎች) ልዩ ሁኔታ ምዝገባ እያከናወኑ ይገኛሉ።

የመራጮች ምዝገባ በአዲስ አበባ

በአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር የመራጮች ምዝገባ በ1600 በላይ በሆኑ ምርጫ ጣቢያዎች ላይ የሚከናውን ሲሆን በዋናነት ከፍተኛ የሰው ቁጥር ባላቸው የጋራ መኖርያ ቤቶች አካባቢዎች የመራጮች ምዝገባ በተለያየ ምክንያት ሲስተጓጎል ነበር ።

ቦርዱ

1. የመራጮች ምዝገባ 1500 ከሞላ በኋላ አዲስ ንኡስ ጣቢያዎችን ለመክፈት የሚወስደው ጊዜ ክፍተት መኖሩን ተረድቷል

2. የምርጫ ክልል አስፈጻሚዎች ምርጫ ጣቢያዎች ላይ የሚያደርጉት ክትትል ማነስ እንደነበር ተገንዝቧል።

3. ንኡስ ጣቢያዎች ከተከፈቱም በኋላ በተደጋጋሚ ቅሬታ የሚነሳባቸው ቦታዎች ላይ በተደረገ የመስክ ቅኝት ጣቢያዎች ቁሳቁስ ሳይደርሳቸው ንኡስ ጣቢያዎችም ሳይከፈቱ ተገኝተዋል (በምሳሌነት በምርጫ ክልል 17 ፣ ምርጫ ክልል 28)

4. የምርጫ ማስፈጸም ሂደቱ ላይ የዝቅተኛ እርከን የመስተዳድሩ አካላት ጣልቃ ገብነት ተስተውሏል።

(ትክክለኛ ያልሆነ ስያሜ ያላቸው ባነሮች በየምርጫ ጣቢያው ማስቀመጥ፣ አስፈጻሚዎችን ስራ መመሪያ መስጠት፣ በምርጫ ጣቢያ መገኘት፣ የተመዝጋቢዎችን ብሎኮች መወሰን...)

5. ምርጫ ጣቢያዎችን ለመክፈት የሚሰጡት ቢሮዎች በተለይ በጋራ መኖሪያ ቤቶች አካባቢ ከጋራ መኖሪያ ቤቶች ቦታዎች የራቁ መሆናቸው ይህም በተለይ በአራብሳ ( ምርጫ ክልል 17)፣ የካ አባዶ ( ምርጫ ክልል 28) የታዩ ናቸው።

እነዚህን ችግሮች ለመፍታት ቦርዱ የወሰዳቸው ዋና ዋና ተግባራት

1. የንኡስ ጣቢያዎችን መከፈት እና የተዘጉ ምርጫ ጣቢያዎችን ሁኔታ አስመልክቶ በከፍተኛ የቦርዱ አመራሮች የተመራ የመስክ ጉብኝት በአዲስ አበባ ተደርጓል፣ ይህም በምርጫ ክልል 17፣ 28፣ 19 …. በመሳሰሉት ቦታዎች ምርጫ ክልሎች እና ጣቢያዎችን አሰራር፣ ክፍት መሆን አለመሆን፣ የመራጮች መዝገብ ቅኝትን ያካትታል። ከቅኝቱ በመለስ ተጨማሪ አዲስ ምርጫ ጣቢያዎችን ከመክፈት በተጨማሪ 30 ንኡስ ምርጫ ጣቢያዎች በሁለት ምርጫ ክልሎች አንዲከፈቱ ተደርጓል። ይህም 1500 ሞልተው ንኡስ ሳይከፈትባቸው የቆዩ ጣቢዎችን ለመክፈት ነው።

2. ሙሉ ሃላፊነታቸው ይህ ሆኖ ሳለ ይህንን ስራ በሚገባ ማስተባበር ያልቻሉ የምርጫ ክልል አስፈጻሚዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ ተወስዷል። ይህም ቁሳቁስ ስርጭትን አለመከታተል፣ ተጨማሪ ምርጫ ጣቢያ ፍላጎቶችን በሚገባ አለማስተናገድ እና የንኡስ ጣቢያ አከፋፈቶችን በአግባቡ አለመፈጸም እነዲሁም የመስተዳድር አካላት ጣልቃገብነት አለመቆጣጠርን ይጨምራል። ሰባት የምርጫ ክልል አስተባባሪዎች የስራ ውል የተቋረጠ ሲሆን የቦርዱን አዲስ አበባ ከተማ የምርጫ ዴስክ ሃላፊም ውላቸው ተቋርጧል። ከዚህም በተጨማሪ የኦፕሬሽን የስራ ክፍል ሽግሽግ እና ተጨማሪ የሰው ሃይል ዝግጅት በማድረግ የውስጥ አቅም የማሻሻል ስራዎች ተሰርተዋል።

3. ለአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር የታዩትን የአስተዳደር ጣልቃ ገብነቶች አስመልክቶ እንዲስተካከሉ ለከተማ መስተዳድሩ አሳውቀናል።

4. የምርጫ ጣቢያዎች እና የመራጮች ቁጥር አለመመጣጠን ባጋጠመባቸው የከተማው ቦታዎች ተጨማሪ ጣቢያዎችን የመክፈት እርምጃ ተወስዷል ( ይህም አዲስ ቦታዎችን ከመስተዳድሩ ጋር በመነጋገር ማስመደብ፣ ቁሳቁስ ማሰራጨት እና አስፈጻሚዎችን መመደብ ይጨምራል)

5. ተጨማሪ የምዝገባ ቀናት መጨመራቸው እነዚህን ችግሮችም ለመፍታት ይረዳል ተብሎ ይታሰባል።

በዚህም መሰረት

በአዲስ አበባ ከተማ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የሚገኙ የመራጮች ምዝገባ ችግሮችን ለመፍታት በአጠቃላይ አዲስ 47 ያህል ምርጫ ጣቢያዎችን ለመክፈት ከከተማ መስተዳድሩ ምርጫ ጣቢያ መክፈቻ ቦታዎችን የጠየቅን ሲሆን፣ የቁሳቁስ ስርጭቶች ቦታዎቹ ዝግጁ በሆኑባቸው አካባቢዎች ተከናውኗል፣ አሁንም እየተከናወነ ነው።

1. በጀሞ ኮንደሚኒየም 15 ተጨማሪ አዲስ ጣቢያዎችን ለመክፈት ከከተማ መስተዳድሩ 15 ለምርጫ ጣቢያነት የሚያገለግሉ ቦታዎች ተመድበው፣ ቁሳቁስ አሰራጭተናል

2. በአቃቂ ቃሊቱ ክፍለከተማ ቱሉዲምቱ ኮንዶሚኒየም 5 ተጨማሪ አዲስ ጣቢያዎችን ለመክፈት ከከተማ መስተዳድሩ ቦታ እንዲያዘጋጅ አሳውቀን 5ቱም ቦታዎች ተዘጋጅተው፣ ቁሳቁስ አሰራጭተናል

3. በአቃቂ ቃሊቱ ክፍለከተማ በገላን ኮንዶሚኒየም 5 ተጨማሪ አዲስ ጣቢያዎችን ለመክፈት ቦታ እንዲዘጋጅ አሳውቀን ከከተማ መስተዳድሩ 5 ቦታዎች ተዘጋጅተው፣ ቁሳቁስ አሰራጭተናል

4. በየካ ክፍለከተማ የካ አባዶ ኮንዶሚኒየም 10 ተጨማሪ አዲስ ጣቢያዎችን ለመክፈት የሚሆን ቦታ እንዲዘጋጅ ከከተማ መስተዳድሩ አሳውቀን እስካሁን 7 ቦታዎች ዝግጁ ሆነው ፣ ቁሳቁስ ስርጭት ዛሬ እየተከናወነ ነው።

5. የካ ክፍለከተማ የካ ሃያት ኮንዶሚኒየም 1 ተጨማሪ ጣቢያ ለመክፈት ከተማ መስተዳድሩ ቦታ እንዲያዘጋጅ አሳውቀን ምላሽ እየጠበቅን ነው

6. በቦሌ ክፍለከተማ ቦሌ ሃያት 1 ተጨማሪ ጣቢያ ለመክፈት ከተማ መስተዳድሩ ቦታ እንዲያዘጋጅ አሳውቀን ምላሽ እየጠበቅን ነው

7. በቦሌ ክፍለከተማ አራብሳ ኮንዶሚኒየም ተጨማሪ 5 ጣቢያ ለመክፈት አሳውቀን ከከተማ መስተዳድሩ 5 ቦታዎች ተዘጋጅተው፣ የቁሳቁስ ስርጭት አጠናቀናል።

8. ቦሌ ክፍለከተማ ሰሚት ኮንዶሚኒየም ተጨማሪ አዲስ 5 ጣቢያ ለመክፈት አሳውቀን ምላሽ እየጠበቅን ነው።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ