የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 6ተኛው አገራዊ ምርጫን ለማከናወን የጊዜ ሰሌዳ ይፋ አድርጎ እየተንቀሳቀሰ እንዳለ ይታወቃል። በጊዜ ሰሌዳው ላይ ከተጠቀሱት ተግባራት መካከል አንዱ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ምልክት መረጣ ሲሆን በጊዜ ሰሌዳው ላይ ከጥር 13-24 ድረስ የምርጫ ምልክት ማስገቢያ እና መወሰኛ ጊዜ እንደሆነ ተቀምጧል። በዚህም መሰረት የምርጫ ምልክት መረጣው እንደሚከተለው የሚከናወን ይሆናል።

1. የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለምርጫ ምልክትነት ሊሆኑ የሚችሉ የተለያዩ ምልክቶችን ያዘጋጀ ሲሆን የፓርቲ ተወካዮች ከተዘጋጁት ምልክቶች ሊወክለኝ ይችላል የሚሉትን ይመርጣሉ።

2. የመረጡት ምልክት በፓርቲያቸው የተያዘ መሆኑን ያስመዘግባሉ። አንድ ፓርቲ ያስመዘገበው ምልክት ከሚመረጡ ምልክቶች ዝርዝር ውስጥ ይወጣል።

3. በቦርዱ ከተዘጋጀው ምልክት ውስጥ የሚፈልጉትን ምልክት ያላገኙ/ወይም የራሳቸውን ምልክት ማስመዝገብ የሚፈልጉ ፓርቲዎች የሚከተሉትን ነገሮች ማሟላት አለባቸው።

- ምልክታቸውን አትመው ለማስመዝገብ ይዘው መምጣት አለባቸው።

- የምልክታቸውን ዲጂታል ፎርማት በፍላሽ ማቅረብ አለባቸው።

- ምልክታቸው በጥቁር እና ነጭ ቀለም ( Black and white) የተዘጋጀ መሆን አለበት።

- ምልክታቸው 2 ሲሜ በ2 ሴሜ መሆን አለበት

- የጥራት መጠኑ (Resolution) 200 – 300 ፒክስል መሆን አለበት

- የፋይሉ መጠን ቢበዛ 200 ኪሎባይት መብለጥ የለበትም

4. የምርጫ ምልክት መረጣው የሚከናወነው ከጥር 13- 18 ሲሆን ቦርዱ ከ18-24 ባለው ጊዜ ውስጥ የማጣራት እና የመወሰን ተግባራትን ያከናውናል።

5. ከጥር 13- 18 ቀን 2013 በሚደረገው የምልክት መረጣ ላይ ማንኛውም ህጋዊ ምዝገባቸውን ያጠናቀቁ ፓርቲዎች በስራ ሰአት ቦሌ ማተሚያ ቤት ፊትለፊት ባለው የሺ ህንጻ 7ተኛ ፎቅ በሚገኘው የፖለቲካ ፓርቲዎች ማእከል ይከናወናል።

6. ይህ የምርጫ ምልክት መረጣ የግል እጩዎችን የማያካትት ሲሆን፣ የግል እጩዎች ምልክታቸው የሚመርጡበት መንገድ ወደፊት በቦርዱ የሚገለጽ ይሆናል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

የጥሪ ማስታወቂያ
ጥር 12 ቀን 2013 ዓ.ም