የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የካቲት 18 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ የምርጫ ጣቢያዎች ዝርዝር ይፋ መሆንን ተከትሎ ከአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የምርጫ ጣቢያዎች ያለአግባብ በሶማሌ ብሔራዊ ክልል መንግስት ስር በሚገኙ ቀበሌዎች ስም ይፋ ተደርገዋል የሚል አቤቱታ ለቦርዱ እንደቀረበ እና የመራጮች ምዝገባ ከመጀመሩ በፊት አቤቱታውን ተመልክቶ ውሳኔ እንደሚሰጥ ማሳወቁ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምርጫ ጣቢያዎችን ሲያደራጅ በአቅራቢያው ያሉ ዜጎች በመራጭነት ለመመዝገብ እንዲሁም ድምጻቸውን እንዲሰጡ ለማስቻል በማሰብ ሲሆን የምርጫ ጣቢያዎች አደረጃጀትም ባለፉት 5 አጠቃላይ ምርጫዎች ተመሳሳይ መስፈርቶችን በመጠቀም ሲከናወን የቆየ ነው። ቦርዱ ለ6ተኛው አጠቃላይ ምርጫ በሚዘጋጅበትም ወቅት በ2007 አጠቃላይ ምርጫ የተጠቀመባቸውን የምርጫ ጣቢያዎችን ታሳቢ በማድረግ በሁሉም ምርጫ በሚደረግባቸው የአገሪቱ ክልሎች ተገማች የመራጮች ቁጥርን ከግምት ውስጥ በማስገባት የተዘጋጁ ናቸው።

እንደሚታወቀው ምርጫ ጣቢያዎች ዜጎች ድምጻቸውን ለመስጠት የሚመቻቹ የመመዝገቢያ እና ድምጽ መስጫ ቦታዎች ሲሆኑ የየትኛውም የመንግስት አስተዳድር መዋቅር አካላት አይደሉም። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም በሚያከናውናቸው የምርጫ ኦፕሬሽን ተግባራት በተለያዩ ደረጃዎች የራሱን መዋቅር የሚያዘጋጅ ሲሆን እነዚህ መዋቅሮች ከመንግሰት ቋሚ መዋቅር ጋር ተመሳሳይነት የላቸውም።

ቦርዱ ከላይ የተጠቀሱትን ጥሬ ሃቆች እና አሰራሮች ከግምት ውስጥ በማስገባት የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የቀረበውን የምርጫ ክልሎች አላግባብ በሶማሌ ክልል ውስጥ በሚገኙ ቀበሌዎች ተጠርተዋል የሚለውን የካቲት 05 ቀን 2013 በተጻፈ ደብዳቤ የቀረበውን አቤቱታ መርምሯል።

ምንም አንኳን ከላይ እንደተጠቀሰው ቦርዱ በ2007 ዓ.ም የተጠቀመበትን የመረጃ ዝርዝር ለ6ተኛው አገራዊ ምርጫ ቢጠቀምም፣ የምርጫ ጣቢያዎች የአስተዳደር ወሰኖችን የሚወስኑ መገለጫዎች ባይሆኑም ቦርዱ ምርጫ በምንም መልኩ የሰላም መደፍረስ ምክንያት እንዳይሆን በማሰብ

  • በጋላእቶ/አዳይሌ
  • በአዳይቱ/አዳይቱ
  • በቴውኦ/አላሌ
  • በጉርሙዳሊ/ዳንሌሄላይ
  • በኡንዳፎኦ/ኡንዱፎ
  • በጋዳማይቱ/ጋርባኢሴ
  • በአፍዓሶ/አፉአሴ
  • በባላእቲ ጎና/መደኒ

ቀበሌዎች ሊከፈቱ የነበሩትን 30 የምርጫ ጣቢያዎች በአካባቢው እንዳይቋቋሙ ወስኗል። በዚህም መሰረት በአካባቢው የሚኖሩ እና የመራጮች ምዝገባ እና የድምጽ መስጠት ሂደት ውስጥ የሚሳተፉ ዜጎች በአቅራቢያቸው ባለ ሌላ ቀበሌ መመዝገብ እና ድምጻቸውን መስጠት የሚችሉ ሲሆን ይህንን ተግባራዊ እንዲያደርጉ ቦርዱ ለምርጫ አስፈጻሚዎቹ ተገቢውን መመሪያ የሚያስተላልፍ ይሆናል።

ይህ ውሳኔ የምርጫ ሰላምን ቅድሚያ በመስጠት በቦርዱ የተወሰነ ሲሆን የመራጮችን የመምረጥ መብት በማይገድብ መልኩ እንዲፈጸም ያደርጋል። በዚህ አጋጣሚም ቦርዱ ሌሎች አካላት የምርጫ ኦፕሬሽንን የምርጫ ጣቢያዎች እና የምርጫ ክልል ቢሮዎቸን አከፋፈት ለቆዩ የአስተዳደራዊ ወሰን ውዝግቦች ግብአት ከመጠቀም እንዲቆጠቡ ያሳስባል።