Skip to main content

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለመራጮች ት/ት ፍቃድ ከተሰጣቸው ሲቪክ ማኅበራት ጋር ሁለተኛ ዙር ውይይት አደረገ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለመራጮች ትምህርት ፍቃድ ከተሰጣቸው የሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች ጋር ሁለተኛ ዙር የውይይት መድረክ አካሄደ። በቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ውብሸት አየለ የተከፈተው መድክ በተከታታይ ለሁለት ቀናት የተካሄደ ሲሆን መጋቢት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. ተጠናቋል። በመጀመሪያ ቀን የተደረገው የውይይት መድርክ የመራጮች ት/ት ፍቃድ አሰጣጥ እና የሥነ-ምግባር መመሪያ ቁጥር 4/2012 ላይ የሠፈሩትን መሠረታዊ ደንቦች ከሲቪክ ማኅበራት ኃላፊነት አንጻር በቦርዱ አመራር አባል አበራ ደገፋ (ዶ/ር) ሲቀርብ፤ በመራጮች ት/ት ወቅት መካተት ያለባቸው ዋና ዋና ጉዳዮች፣ ለሲቪክ ማኅብራት የተዘጋጀ ማስታወሻ፣ ሪፖርት ማድረጊያ ቅጽ እንዲሁም የሥነ-ምግባር ደንቡን የተመለከቱ ጉዳዮች በቦርዱ የሲቪክና የመራጮች ትምህርት ክፍል ባልደረቦች አማካኝነት ተብራርቷል። የመራጮች ት/ት አሰጣጥ ላይ የኮቪድ 19 መመሪያ እና የሥነ-ምግባር ድንብን ማስተዋወቅ ሌላው የመጀመሪያው ቀን ውይይት አጀንዳ ሲሆን በቦርዱ የኮቪድ 19 አስተባባሪ አማካኝነት ማብራሪያ ተሰጥቶበታል። ማብራሪያዎቹን ተከትሎ ከተሣታፊዎች ለቀረቡት አስተያየቶች በቦርድ አመራሩ አበራ ደገፉ (ዶ/ር) እንዲሁም በቦርዱ የሥራ ክፍሎች መልስ ተሰጥቶባቸዋል።

አካታች የሆነ የመራጮች ት/ት አስፈላጊነት፤ ከሥልጠናው የሚጠበቁ ውጤቶች እና ምርጫውን አካታች ለማድረግ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች በሁለተኛው ቀን የውይይት መድረክ ላይ ትኩረት ከተደረገባቸው አጀንዳዎች ውስጥ ሲሆኑ፤ የሥርዓተ-ፆታና የአካል ጉዳተኞች አካታችነት መተግበሪያ ዘዴዎች እንዲሁም ከሥነ-ምግባር መመሪያ አኳያ የሲቪክ ማኅበራት ኃላፊነትን በተመለከተ በቦርድ የሥርዓተ -ፆታ እና አካታችነት ክፍል ባልደረባ ሲቀርብ፤ የመራጮች ት/ት አካታችነት አስመልክቶ ዓለም ዐቀፍ ተሞክሮ ባላቸው ባለሙያ ተጨማሪ ግንዛቤ ማስጨበጫ ተሰጥቶበታል። ማብራሪያዎቹን ተከትሎ ከተሣታፊዎች ጋር ውይይት ከመደረጉ በተጨማሪ ተሣታፊዎቹ በቡድን ሆነው እንዲወያዩና ሀሳባቸውን እንዲያጋሩ ተደርጎ የፕሮግራሙ ማብቂያ ሆኗል።

Share this post