Skip to main content

ኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከኦሮሞ ነጻነት ግንባርን ( ኦነግ) አመራር አባላት የቀረበለትን አቤቱታዎች አስመልክቶ የሰጠው ውሳኔ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ፓርቲ አመራር አባላት የአመራር ለውጥ እና እገዳን አስመልክቶ የተለያዩ አቤቱታዎች ሲደርሱት እንደነበር ይታወቃል፡፡
በአንድ በኩል በእነ አቶ አራርሶ ቢቂላ ነሐሴ 1 ቀን 2012 ዓ.ም. በቁጥር 06/ABO/12 እና 7/08/12 05/03/19 በቁጥር 08/ABO/12 በተፃፉ ሁለት ደብዳቤዎች የፓርቲው የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በፓርቲው ሊቀመንበር በአቶ ዳውድ ኢብሳ ላይ የእግድ ውሣኔ አስተላልፏል ሲሉ ለቦርዱ በማሳወቅ ቦርዱ ውሳኔውን እንዲያጸድቅላቸው ጠይቀዋል፡፡

በሌላ በኩል አቶ ዳውድ ኢብሣ በ08/10/2020 (እ.ኤ.አ) በቁጥር 0211/xly/abo/2020 በተፃፈ ደብዳቤ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት በሆኑት አቶ አራርሶ ቢቂላ፣ አቶ ቶሌራ ተሾመ፣ አቶ አቶምሣ ኩምሣ እና የብሔራዊ ምክር ቤት አባላት የሆኑት አቶ ቀጄላ መርዳሳ እና አቶ አርብቾ ዲማ እስሚቀጥለው ጠቅላላ ጉባኤ ድረስ ከኃላፊነታቸው ታግደው እንዲቆዩ ስለተወሰነ ይኀው ውሳኔ በቦርዱ እውቅና እንዲሰጠው ጠይቀዋል፡፡  የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ይህንኑ በፓርቲው አባላት መኻከል የተፈጠረውን ያለመግባባት የሚያስረዱትን ከዚህ በላይ የተገለፁትን ደብዳቤዎችና ሌሎች የጽሑፍ አቤቱታዎችን መስከረም 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ መርምሯል፡፡ በፖለቲካ ፓርቲ አባላት መኻከል አለመግባባት ሲከሰት እና ለቦርዱ አቤቱታ ሲቀርብለት በአዋጅ ቁጥር 1162/11 አንቀፅ 74 ንዑስ አንቀፅ 6 መሠረት ጉዳዩን ተመልክቶ የውሣኔ ሃሣብ የሚያቀርብ የባለሙያዎች ጉባኤ የማቋቋም ሥልጣን አለው፡፡

በመሆኑም በእነ አቶ ዳውድ ኢብሣ የሚመረጥ/የምትመረጥ አንድ፤ በእነ አቶ አራርሶ ቢቂላ የሚመረጥ/የምትመረጥ ሌላ አንድ፤ እንዲሁም እነዚህን ሁለት በባለጉዳዮቹ የሚመረጡትን ባለሙያዎች በሰብሳቢነት የሚመራ/የምትመራ ሌላ አንድ ባለሙያ ቦርዱ መርጦ በመመደብ የባለሙያዎች ጊዜያዊ ጉባኤ እንዲቋቋም መስከረም 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ ወስኗል፡፡ በዚህም መሰረት በሁለቱ አካላት እና በቦርዱ የተመረጡ ባለሞያዎች ጉዳዮን አጣርተው በሚያቀርቡት የውሳኔ ሃሳብ ላይ ተመስርቶ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የመጨረሻ ውሳኔ የሚሰጥ መሆኑን ያሳውቃል፡፡ 


የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 
መስከረም 29 ቀን 2013 ዓ.ም

Share this post