Skip to main content

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ስጋት ከግምት ውስጥ ያስገባ ምርጫ ለማከናወን እየሰራ ነው

ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም ሊካሄድ የነበረው 6ተኛው አጠቃላይ ምርጫ በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ስጋት ምክንያት ሊከናወን አለመቻሉ ይታወሳል። ቦርዱ በአሁኑ ወቅት በምርጫ ወቅት የኮቪድ-19 ስርጭትን በመከላከል ረገድ አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶችን ለማከናወን ይረዳ ዘንድ የኮቪድ-19 አስተባባሪ ቀጥሮ የተለያዩ ተግባራትን እየፈጸመ ነው።

ከእነዚህም ውስጥ በምርጫ ወቅት የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር አዘጋጅቶ ያጸደቀው መመሪያ አንዱ ሲሆን በዚህ መመሪያ ዙሪያ ከፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጋር ተደጋጋሚ የጋራ ምክክር መድረክ አከናወኗል። ከዚህም በተጨማሪ የሰራቸው ስራዎች የሚከተሉት ናቸው።

1. ቦርዱ ባወጣው መመሪያ መሰረት ለመራጮች ትምህርት የሚያገለግል የኮቪድ- 19 መተላለፊያ እና መከላከያ መንገዶች፣ በሁሉም የምርጫ እንቅስቃሴዎች የሚተገበሩ የኮቪድ-19 ቅድመ ጥንቃቄ እርምጃዎች እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተግባር እና ኃላፊነቶችን የሚገልጽ ማኑዋል በማዘጋጀት የመራጮች ትምህርት መርሀ ግብር ውስጥ አካትቷል።

2. በዕጩዎች እና መራጮች ምዝገባ እና በድምጽ አሰጣጥ ሂደት ላይ የሚተገበሩ የኮቪድ-19 ቅድመ ጥንቃቄ እርምጃዎችን በዝርዝር በማስቀመጥ የምርጫ አስፈጻሚዎች የስልጠና ማኑዋሎች ላይ እንዲካተት ተደርጓል።

3. ለምርጫ ወቅት የሚያገለግሉ የኮቪድ-19 የግል መከላከያ ቁሳቁሶች ማለትም የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብሎች እና የእጅ ሳኒታይዘሮች ምርጫ ቦርድ ለሚያሰማራቸው አሰልጣኞች እና የምርጫ ክልል ጽ/ቤት እና የምርጫ ጣቢያ ምርጫ አስፈጻሚዎች ተደራሽ ለማድረግ ግዥዎችንም ፈጽሟል።

4. ለእጩዎች ምዝገባ ለተከፈቱት የምርጫ ክልል ጽ/ቤቶች፣ ለስልጠና ቦታዎች አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብሎች እና የእጅ ሳኒታይዘሮች አሰራጭቷል።

5. የኮቪድ ወረርሽኝን ለመቆጣጠር መወሰድ ያለበትን ጥንቃቄ እና ስነምግባር ደንብ አዘጋጅቶ ተወዳዳሪ እጩዎች እንዲፈርሙት አድርጓል።

6. ከቦርዱ ጋር አብረው የሚሰሩ የመራጮች ትምህርት የሚያስተምሩ ሲቪል ማህበራት፣ ምርጫ ለመታዘብ የሚንቀሳቀሱ ታዛቢዎች፣ ጋዜጠኞች ሊያደርጉት የሚገባውን ጥንቃቄ እና ስነምግባር ደንብ በማዘጋጀት እየሰራ ይገኛል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በምርጫ ወቅት የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመከላከል በሚያደርጋቸው እንቅስቃሴዎች አጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን ሰፊ በሆነው የምርጫ ተግባር የሚንቀሳቀሱ አካላትም በፈረሙት የስነ ምግባር ደንብ እና ቦርዱ ባጸደቀው መመሪያ መሰረት መሆን እንዳለበት ያስገነዝባል። መመሪያውን ለማግኘት ሊንኩን ይጫኑ link text

Share this post