ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተላለፈ ለባለሞያዎች ዝርዝር (Professionals roster) ውስጥ ማካተቻ ጥሪ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባለፉት ስድስት ወራት የተለያዩ ተቋማዊ ለውጦችን ለማካሄድ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ከነዚህም ለውጦች መካከል ዋናው ተቋሙን ከፍተኛ አቅምና ቁርጠኝነት ያለው የሰው ሃይል እንዲኖረው ጥረት ማድረግ ነው፡፡
በዚህም መሰረት የቦርዱ ጽ/ቤት በተለያዩ ሞያዎች የከፍተኛ ክህሎት ባለቤት የሆኑ ግለሰቦችን ግለታሪክ (ካሪኩለም ቪቴ) መሰብሰብና የባለሞያዎች ዝርዝር በማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖም ሲገኝ በበጎ ፍቃደኝነት፣ በጊዜያዊ ኮንትራት ስራ፣ እንዲሁም በቅጥር ከተቋሙ ጋር አብረው መስራት የሚችሉበትን መንገድ ለማመቻቸት ይፈልጋል::
በመሆኑም ከስር በተጠቀሱት የስራ ዘርፎች ላይ ክህሎት ያላችሁ፣ ለገለልተኛ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ግንባታ ጥልቅ ቁርጠኝነት ያላችሁ እና በአቅማችሁ በተለያየ ሁኔታ ምርጫ ቦርድን ልትደግፉ እና አብራችሁ ልትሰሩ ፍላጎት ያላችሁ ግለሰቦች ሲቪያችሁን እና ለምን ከምርጫ ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ላይ መስራት እንደፈለጋችሁ እንዲሁም በምን በምን መልኩ አስተዋእጾ ማድረግ እንደምትፈልጉ የሚያሳይ ከአንድ ገጽ ያልበለጠ ሸኚ ደብዳቤ (Personal statement) ጋር በማያያዝ በኢሜል አድራሻችን electionsethiopia [at] gmail.com መላክ ትችላላችሁ፡፡

የሚፈለጉ የክህሎት አይነቶች

1. የስራ አመራር ከፍተኛ ሃላፊ/ባለሞያ/ Office manager/administration (የፕሮጄክት አስተዳደር እውቀት እና የመንግስትና መንግስታዊ ያልሆነ የስራ አመራር፣ አስተዳር እና ፋይናንስ ስራ ልምድ ያለው/ያላት፣ የህግና የፓለቲካ ሳይንስ እውቀትና ልምድ ያላት/ያለው)

2. የፋይናንስ ባለሞያ (መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ በመስራት ልምድ ያለው/ያላት፣ አለም አቀፍ ድርጅቶንና የመንግስት የፋይናንስ        አሰራርን የምታውቅ/የሚያውቅ)

3. የሰው ሃይል አስተዳደር ባለሞያ /Human resource management/

4. ፕሮጀክት ማኔጅመንት /Project management/

5. የፕሮጀክት ማስተባበር  /Project coordination/

6. ኤቨንት ኦርጋናይዘር /Event organizer/

7. የአይቲ እና የኤሌክትሪካል ባለሞያ (በመሰረታዊ አይቲ ድጋፍ፣ ሃርድዌር ቴክሻን፣ ኔትወርኪንግ፣ ዳታቤዝ፣ ሴኩሪቲ…)

8. የህግ ባለሞያ (በፓለቲካ ፓርቲዎች ድጋፍ፣ በህግ እና ደንቦች ረቂቅ ዙሪያ ፍላጎትና ክህሎት ያላት/ያለው)

9. የጥናት ባለሞያ /researchers/

10. የሎጂስቲክስ እና አቅድ ባለሞያ /Logistics and planning/

11. የሚዲያ ባለሞያ (ሶሻል ሚዲያ፣ የሚዲያ ክትትል፣ የኤዲቲንግ፣ ግራፊክስ፣ የፎቶና የቪዲዮ ኤዲቲንግ የመሳሰሉት እውቀት ያላት/ያለው)

12. የግጭት አፈታት እና የጸጥታ ጥናት ባለሞያ

13. በሌላ በማንኛውም የስራ ዘርፍ እና ማማከር አገልግሎት ለምርጫ ቦርድ አይነት ተቋማት አስተዋእጾ ይሆናል ብለው ያመኑበት ማንኛውም አይነት ሞያ/ክህሎት

ማስታወሻ - ይህ ማስታወቂያ የስራ ቅጥር ማስታወቂያ ሳይሆን የባለሞዎች ዝርዝር ማዘጋጃና ክህሎት ማሰባሰቢያ ሲሆን ቦርዱ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ለባለሞያዎች ጥሪ ያደርጋል፡፡ ይህ ጥሪ የሚመለከተው የምንም አይነት የፓለቲካ ፓርቲ አባላት ላልሆኑ ግለሰቦች ሲሆን፣ በደብዳቤያችሁ ላይ በበጎ ፍቃደኝት ለማገልገል ያላችሁን ፍላጎት እንድትገልጹ ቦርዱ በአክብሮት ይጠይቃል፡፡

የስራ ማስታወቂያ
ሐምሌ 10 ቀን 2010 ዓ.ም.