የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነፃ የዓየር ሰዓት ድልድል የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት አካሄደ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዛሬ መጋቢት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነፃ የዓየር ሰዓት ድልድል የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት አካሄደ። የመድረኩን የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ ሲሆኑ በንግግራቸው ነፃ ዓየር ሰዓት ድልድሉን በዐዋጁ መሠረት ቦርዱ ከመገናኛ ብዙ`ኃን ባለሥልጣን ጋር በመሆን ለሣምንታት ሲያስተባብር እንደነበር ገልጸው፤ የሰዓት ድልድሉ ፖለቲካ ፓርቲዎች ፕሮግራማቸውንና ፖሊሲዎቻቸውን እንዲያስተዋውቁ፣ የግል ዕጩዎችም አማራጭ ሀሳባቻቸውን እንዲያጋሩና የምርጫ ቅስቀሳ እንዲያደርጉ፣ ከመራጩ ጋር እንዲተዋወቁ ዕድል የሚሰጣቸው መሆኑን ተናግዋል። ይፋ የተደረገው ነፃ የዓየር ሰዓትን የተመዘገቡ 46 ፖለቲካ ፓርቲዎችና የግል ዕጩዎች በኃላፊነት ስሜት እንዲጠቀሙበት በአፅንዖት አሳስበዋል።
የባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ ዳይሬክተር ኃይማኖት ዘለቀ በበኩላቸው ነፃ የዓየር ሰዓት ድልድሉ በ50 መገናኛ ብዙኃን ላይ እንደተደለደለ ገልጸው፤ ድልድሉ በሕጉ መሠረት የምርጫውን ነፃ፣ ገለልተኛና ፍትሐዊነት በሚያረጋግጥ መልኩ እንደተሠራ ተናግረዋል። በሕዝብና በንግድ መገናኛ ብዙኃን ላይ የተደረገው ድልድሉ በ24 ሬዲዮ፣ በ20 ቴሌቪዥኖች እና በስድስት ጋዜጦች ላይ መሆኑን ገልጸው፤ በሥራቸው ያሉ ቻናሎችና በቋንቋ ሲታሰብ ድልድሉ በ66 ቻናሎች እንደሚሆን ተናግረዋል።
የመክፈቻ ንግግሩን ተከትሎ የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ተስፋዬ ንዋይ “የፖለቲካ ፓርቲዎች እና የግል ዕጩ ተወዳዳሪዎች የመገናኛ ብዙኃን አጠቃቀምና ድልድል” በተመለከተ ሰፊ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን፤ እሻቸውን ተከትሎም “የነፃ የዓየር ሰዓት ድልድል ማከናወኛ ሲስተምን የተመለከተ ማብራሪያ” ከመገናኛ ብዙኃኑ በላይ ቅጣው አብራርተዋል። በመጨረሻም በለማው ሲስተም አማካኝነት የዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ተከናውኗል።
ቦርዱ በቅድመ ምርጫ ተግባራቱ ከሚያከናውናቸው በርካታ ሥራዎች ውስጥ “በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ-ምግባር ዐዋጅ ቁጥር 1162/2011 አንቀጽ 44 (3) እና “በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ማቋቋሚያ ዐዋጅ ቁጥር 1133/2011 አንቀጽ 7 እንዲሁም “በኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን በመገናኛ ብዙኃን ዐዋጅ ቁጥር 1238/2013 አንቀጽ 71 (4) እና (5) በተሰጣቸው ሥልጣን መሠረት የፖለቲካ ፓርቲዎችን “የመገናኛ ብዙኃን አጠቃቀም” በጋራ ተፈጻሚ ማድረግ ተጠቃሽ ነው።